Friday, December 1, 2017

ለማይቀረው ለውጥ፥ የለውጥ ሐዋርያ ለመሆን እንታገል!!



   በአገራችን ኢትዮጵያ አሁን ያለው አፋኝ ስርዓት ተገርስሶ የአገራችን ህዝቦች በሰላምና በመፈቃቀር የሚኖሩበት ጊዜ የሚመጣ መሆኑን ለማወቅ ነብይ መሆን አይጠይቅም። የወያኔ ኢህአዴግ ስርዓት የኢትዮጵያ ህዝብ ጠላት ሆኖ ብሄር ከብሄር ጋር እያጣላን እንዳለ፤በብልሹ ቢሮክራሲያዊ አሰራርና ፖሊሲ ምክንያት በድህነት ተዘፍቀን እንድንኖር እያደረገን እንዳለ፤ዴሞክራሲያዊና ሰብዓዊ መብቶቻችንን አፍኖ እስርቤትን ቤታቸው አድርገው የሚኖሩ ዜጎች በዝተው እንዳሉ ከዚህ ባለፈም ሞትና ስቃይ ተበራክቶ እየቀጠለ እንዳለ ከማንም የተደበቀ አይደለም።
   ለዚህ አንጃቦብን ላለው የጥፋት አደጋና መበታተን መፍትሄ ለመስጠት ደግሞ የኢትዮጵያ ህዝብ ምንም እንኳን መደራጀትና መጠናከር የሚያስፈልገው ቢሆንም በጋለ አገራዊ ትግል ተጠምዶ ከማንኛውም ወቅት በበለጠ ጥፊውን እያመረረ ስርዓቱን ደምበርበር ከሚያደርገው ረጅም ጊዜ አድርጓል። ይህ እየተካሄደ ያለው ትግል ደግሞ ሳይንሳዊና የተደራጀ እንዲሆን ውጤቱ ደግሞ እንደተለመደው በብልጦች እጅ እንዳይገባ ሰላማችንና እድገታችን ገሃድ እንዲሆን የምሁር ሃይሉ ሚና ወሳኝ ሆኖ ይገኛል። 
  የአገራችን ምሁር ሃይል አገርህን ጥለህ ወደ ስደት በማምራት ለግልህ ብቻ ከመኖር ወጥተህ፣ ሳይማር ላስተማረህ ህብረተሰብ እንድትክስ የብዙዎች የአገርህ ልጆች ምኞት ነው። ይህ ተፈጥሮ ያለው የጥፋትና የልማት መድረክ ሁለት መንታ መንገድ ይዞ ይገኛል። ይህ መድረክ በንቃትና በሳይንሳዊ ከያዝነው የለውጥ ዘመናችን ይሆናል። ካልተጠቀምንበት ደግሞ ካለንበትም ሊብስ ይችላል።
መንግስት አገሪቱን ሊመራት የማይችልበት ደረጃ ላይ ደርሶ ይገኛል። ህዝቡ ደግሞ ጭቆና አንገፍግፎት አንባገነኖችን አሻፈረኝ ብሎ ተቃውሞው ጫፍ ላይ ደርሶ ይገኛል። ይህ ሁሉ ሆኖ እያለ ተቃውሞኣችን በአንድነት እንዲጠነክርና ጥፊያችን እንዲበረታ በልብ አንድ ልንሆን ይገባናል። በዚህ ላይ የምሁራን ድርሻ ከፍ ያለ መሆን አለበት ብቻም ሳይሆን አሁን ያለውን ጉዞ ወደ መጨረሻው ምዕራፍ እንዲያደርሱት ጊዜ ሳያልፍ ዛሬ መነሳት ብቻ ሳይሆን መሮጥ ወቅቱ የሚጠይቀው መድረክ ነው።
በተለይ ደግሞ በከፍተኛ የትምህርት ተቋማት የሚገኙ ተማሪዎች የቀደምት ዩኒቨርሲቲ ተማሪዎችን ታሪክ ማጥናት ያለባቸው ይመስላል። እንደነ ጥላሁን ይግዛው ያሉ የመሳፍንት ልጆች እያሉ ግን ደግሞ ከጭቁን ህዝብ ጋር ወግነው መስፍንነትን በመቃወም እንዲሁም ለብሔር ብሔረሰቦች መስዋዕት የሆኑ የኢትዮጵያ ልጆችን በመንፈስ ወደ ኋላ ተመልሰን ማየት ያስፈልገናል።
የሶማሌ ተወላጅ ሆነህ በጅማ፤በአምቦ ዩኒቨርሲቲ በነፃነት ኮርተህ ልትማርበት የማትችልበት ምክንያት ምንድን ነው? የኦሮሞ ክልል ተወላጅ ሆነህ በኢትዮጵያ ሶማሌ ሄደህ ለመማር የሚያስፈራህ ያለው ችግር ምንድን ነው?ካድሬዎችና ከፍተኛ የወያኔ ኢህአዴግ አመራሮች የአንድነታችንና የልማታችን መናጋት ጠንቅ መሆናቸውን አምነን ለምን ትግላችንን ከጫፍ የማናደርሰው። ተጋሩ በደሉን፤ በሶማሌ ተጨፈጨፍን፤በኦሮሞ ተገደልን የሚል በስርዓቱ ተወዳጅ የሆኑ ሐሳቦች ከምንደጋግም፤እንቢታችን በሶማሌ ሄጀ አልማርም ወይም ወደ ኦሮሚያ አልሔድም ሳይሆን በወያኔ ኢህአዴግ ስርዓት አልመራም የሚል መራራ ተቃውሞ ልንሰማ ይገባል።   
  የሚቃወመው የህብረተሰብ ክፍል ጉልህ ተቃውሞ ከማይታይባቸው በልዩ ስለተበደለ አይደለም። የወያኔ ኢህአዴግ አለንጋ በመላ አገራችን ተዘርግቶ ሁሉንም ህብረተሰብ እያደማ ነው የሚገኘው። የሚቃወመው ግን የነቃና መብቱንና ግዴታውን ለይቶ የሚያውቅ ነው። የማይቃወመው ስላልተበደለ ነው በስርዓቱ ጥቅም ስላለው ነው የሚል አቋም ከያዝን በስህተት አረዳድ ውስጥ ገብተናል ማለት ነው። ሰብዓዊና ዴሞክራሲያዊ መብቶቹን በአግባቡ ያልተረዳ ከሆነ ለዚህ ጊዜ የሚመጥን ፖለቲካዊ ንቃት እየሰጠን በለውጡ መስመር እንዲታቀፍ እናድርገው። በሚደረገው ተቃውሞ ጥርጣሬ ካለው ደግሞ ተቃውሞኣችን ለእውነተኛ እኩልነትና እድገት እንደተሰለፍን አሳምነን ደጋፊያችን እንዲሆን እንጣር። ህዝብ እንደህዝብ በጠላት ማጥመቅ ለማንም አይጠቅምም። ህዝብ በሙሉም ጠላት ሊሆን አይችልም።
ስለዚህ በመላ አገራችን ያለህ ወጣት ሃይል በለውጥ ሃይል እየጋለብህ በወርቃዊ ቀለም ታርክህን ወርቅ፥ ለማይቀረው ለውጥ የለውጥ ሃዋርያ እንድንሆን ደግሞ እንታገል።

        

No comments:

Post a Comment