Sunday, December 31, 2017

የህዝብን ወሣኝነት ለማረጋገጥ እንረባረብ!!



   የህዝብን ወሣኝነት ማክበር ማለት የህግ የበላይነትን ማረጋገጥ ማለት ነው። የህግ የበላይነትን ማክበር ማለት ደግሞ ዋስትና ያለው ሰላም ማስፈን ማለት ነው። የሰላም ዋስትና መኖር ደግሞ ዜጎች ከቦታ ቦታ ተንቀሳቅሰው ያለምንም ስጋትና ጥርጣሬ በልበ ሙሉነት ከአገራቸው እህትማማች ህዝቦች ጋር አብረው እንዲሰሩና መኖር እንዲችሉ የሚያስችላቸው ምቹ ሁኔታ መፍጠር ነው።
   የህዝብን ሉኣላዊነት በመጨፍለቅ፤ ህግ በመጣስ፤እኔ ያልኩህን ብቻ ስማ ከእኔ በላይ ወሣኝ የለም በሚል መንገድ ተከትሎ፣ ብሎም የአገርንና የህዝብን ሃብት ለግለዊ ሙሰኛ መሪዎችና ተባባሪዎቻቸው አጋልጦ አገር እንደ ሃገር ህልውናዋ በጥያቄ ምልክት ውስጥ እንዲገባ ያደረገ ስርዓት ግን፣ የህዝብን ወሣኝነት አያረጋግጥም። ምክንያቱም ህግ እየጣሱ የህዝብን ሉኣላዊነት ማረጋገጥ ስለማይቻል። 
   የህዝብን የበላይነትና ወሣኝነት ማረጋገጥ ማለት በሌላ ገፅታ የብሔር ብሔረሰቦችን ዋስትና እና አንድነት ማጠናከር ማለት ነው። የብሔሮች አንድነት፤መከባበር፤መተሳሰብና ፍቅር ደግሞ ሠላሟ የተረጋጋ የበለፀገች ሃገር መገንባት ማለት ነው። 
   ይህንን የህዝብን የበላይነትና ወሣኝነት ወደ ጎን በመወርወር አገርን በግላዊ ይዘቱ አትኩሮ እየመራ፤በማደናገር በጥፋት ጎዳና እየተንሳፈፈ ሲያውክ የቆየውና ያለው የወያኔ ኢህአዴግ ቡድን፣ ዛሬ ላይ ሲቀብራቸው የቆዩት እውነታዎች እየፈነዱ ለመፍታት ተቸግሮ እርስ በርሱ ሲበላላ ይውላል።
   “እውነት ትከራለች እንጂ አትበጠስም” እንደተባለው፣ ከህዝብ ፍላጎት፤ጥቅምና ጥያቄ ወጥቶ በፀረ ዴሞክራሲ ተግባሮችና እኔነት ተሰማርቶ በሙስናና ብልሹ አስተዳደር ተዘፍቆ ሲጓዘው የመጣውና ያለው መንግስታዊና ቡድናዊ አስተዳደሩ፣ ወደ ውድመትና መበታተን አደጋ እንዳጋለጠንና ለእኛ ኢትዮጵያውያን ብቻም ሣይሆን ሰላማችንን፤ ጥሩ ዝምድናችንን እና ጉርብትናችንን የሚመኙ ወዳጆቻችንን የአካባቢያችንን ህዝቦችም ጭምር ስጋት ውስጥ እንዲወድቁ አድርጓል።
   ይህ ደግሞ በአንድ ጊዜ የተፈጠረ አደጋ ሳይሆን ከመጀመሪያ ጀምሮ የተከተለው አውዳሚ ፖሊሲው፣ እየተገበረው የመጣው ፀረ ህዝብና የአገራችን ብሄር ብሔረሰቦች የአንድነት ፀር በመሆኑ፣ይህንን ሰይጣናዊ ጉጅሌ ተግባራቱን ኮንነን ኢትዮጵያውያን በጋራ አንፃሩ እንዳንነሳ በሚፈጥራቸው መዘዞች እርስ በርሳችን ሲያጋጨን ቆይቷል፣ አሁንም እያቃቃረን ይገኛል።
    ለዚህ እየተከተለው የመጣውና ያለው አውዳሚ፤ ፀረ ዴሞክራሲና የህግ የበላይነትን ጥሰት ለመቆጣጠር ብሎ እራሱ ባቋቋማቸው ተቋሞችም ሓቁን እያዳፈኑ የቡድኑን ልሳን በሎሌነት በመድገም የህዝባዊ ሃላፊነታቸውን ረስተው በይምሰል ስራዎችና ተግባሮች እንዲጠመዱ አድርጓቸዋል።
   የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ወይም ደግሞ ፓርላማ ከተቋሞቹ አንዱ ሲሆን ለስም የበላይ ስልጣን ያለው የህዝብ ወኪል መሆኑን ህገ መንግስቱ ጭምር እውቅናና ስልጣን እንደሰጠው ተደንግጓል። 
   ነገር ግን ቡድኑ የህግ የበላይነትን እየጣሰ የህዝብን ሉኣላዊነት እየደቆሰ የዜጎችን ሰብዓዊና ዴሞክራሲያዊ መብቶች አፍኖ እንደፍላጎቱ እየደለቀ፣እነዚህ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት እያዩ ኃላፊነት ወስደው ተግባሩን የሚኮንኑበት ሁኔታና የህግን የበላይነት ለማረጋገጥ የሚያደርጉት ሂደትስ አለ ወይ? ካለስ የዜጎች ህይወት በየቀኑ እየተቀጠፈ፣ ወንጀለኛው ወደ ህግ ፊት ቀርቦ አስተማሪ የሆነ እርምጃ ለምን እንዲተገበር አላደረጉም?
   ይህ በስም ህዝብን ወክሎ ስልጣኑን እንዳይቀማ በስጋት ተውጦ የሚኖር ምክር ቤት ከመሆን አልፎ ለህዝብ ፍላጎት፤ጥቅምና ዋስትና ጠበቃ ሆኖ ሊሰራ አልቻለም። “ነገር ለአምጭው…” እንደተባለው፣ ዛሬ ለራሱ ለምክር ቤቱ፤ገዥው ስርዓት፤ ህዝብና ሀገር ለአደጋ በተጋለጠበት፣ ኦሮሚያ በአዲስ አበባ ዙሪያ ሊኖራት የሚገባ ጥቅም ላይ ለመወያየት የተጠራው ስብሰባ ያለስምምነት ሲበተን ታይቷል። ቀድሞውንም ህዝብ ያልተሳተፈበት ረቂቅ በከፍተኛ ባለስልጣናት ሊተገበር አይችልም። ስለዚህ የህዝብን ወሣኔ እና ፍላጎት ለማክበርና ለመተግበር ልንረባረብ ይገባል።

1 comment: